Saturday, August 2, 2014

ጥቂት ስለ ደራሲ እና መምህር ሲሳይ ንጉሱ


   በ1951 ዓ.ም እዚሁ አዲስ አበባ ውስጥ ደጃች ውቤ /ውቤ በረሃ/ ነው የተወለደው፡፡ አንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በባልቻ አባነፍሶ ፣ ሁለተኛ ደረጃን ደግሞ በአዲስ ከተማ አጠቃላይ ት/ቤት ተከታትሏል፡፡ከዚያም በ1974 ዓ.ም አስመራ ዩኒቨርስቲ ገብቶ በስነ ፅሁፍ እና ቋንቋ በ1977 ዓ.ም የመጀመሪያ ዲግሪውን አግኝቷል፡፡ 11ኛ ክፍል እያለ “ጉዞው” የተሰኘ ኖቬላን የመጀመሪያ ስራው አድርጎ አሳትሟል፡፡ይህንን ጨምሮ 6 ያህል መፅሃፍትን እስካሁን ለአንባቢያን አድርሷል፡፡ “ሰመመን” የተሰኘው የረጅም ልብ ወለድ ድርሰቱ ከፍተኛ ተነባቢነትን በአጭር ጊዜ ውስጥ ያገኘለት ስራው ሲሆን በወቅቱም 60 ሺ ያህል ቅጂዎች ተሸጠውለታል፡፡በ1978 ዓ.ም የታተመው እና 378 ገፆች ያሉት “ሰመመን” በዩኒቨርስቲ ህይወት ዙሪያ እና በፍቅር ታሪክ ላይ ያተኩራል፡፡ መፅሃፉ የተፃፈው ደራሲ ሲሳይ ንጉሱ በአስመራ ዩኒቨርሰቲ የ 3ኛ አመት ተማሪ እያለ ነበር ፡፡

  የደራሲው ስራዎች፡-
1.  ጉዞው ( ኖቬላ ) – 1975 ዓ.ም
2.  ሰመመን ( ልብ ወለድ ) – 1977/8 ዓ.ም
3.  ግርዶሽ ( ልብ ወለድ ) –  1981 ዓ.ም
4.  ትንሳኤ (  ››     ›› )  –  1983 ዓ.ም
5.  የቅናት ዛር ( ››    ›› ) –  1988 ዓ.ም
6.  ረቂቅ አሻራ ( ››   ›› ) –  1995 ዓ.ም


   “ሰመመን” የተሰኘው ድርሰቱን በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ሲያሳትም፤ ግርዶሽ፣ ትንሳኤ፣ የቅናት ዛር እና ረቂቅ አሻራን በአርቲስቲክ እና ሜጋ ማተሚያ ድርጅቶች በግሉ ነው ያሳተማቸው፡፡ በ1983 ዓ.ም አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት የታተመውን “ትንሳኤ” መፅሃፍ መታሰቢያነቱን በፋሽስቶች “ቀይ ሽብር” ለወደቅው /ለሞተው/ አጎቱ ለታምሩ ተክሉ አድርጓል፡፡ በዚሁ ማተሚያ ቤት በ 1995 ዓ.ም የታተመው “ረቂቅ አሻራ” ደግሞ ማስታወሻነቱን ለባለቤቱ ብስራት አሰፋ እና ለልጁ ትንሳኤ ሲሳይ ይሁንልኝ በማለት ነው ለአባቢያን ያበረከተው፡፡ አስመራ ዩኒቨርሰቲ እያለ የስነ ፅሁፍ እና የቲያትር ክበብ መስርቶ ይንቀሳቀስ ነበር፡፡ የ ’’ብዕር አምባ’’ በሚል ስያሜ፡፡ የ4ኛ አመት የዩኒቨርሰቲ ተማሪ እያለም ‘’ስዊት ዲስ ኦርደር’’ የሚል ቲያትር ደርሶ ለእይታ አብቅቷል፡፡ ቲያትሩ በአሉላ አባ ነጋ አዳራሽ የታየ ሲሆን በወቅቱም በተመልካች ዘንድ ተወዳጅ ነበር፡፡ በዚህ ቲያትር ላይ ሲሳይም በተዋናይነት ተሳትፏል፡፡

  አስመራ ዩኒቨርሰቲ ለ2 አመት ካስተማረ በኋላ ሙሉ ጊዜውን ለስነ ፅሁፍ በማድረግ ግርዶሽ የተሰኘውን ድርሰቱን አሳትሟል፡፡ ይህ መፅሃፍም ከ “ሰመመን” ቀጥሎ ከፍተኛ ሽያጭ ነበረው ፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥም 40 ሺ  ቅጃዎች ተሸጦለታል፡፡


  ደራሲና መምህር ሲሳይ ንጉሱ ለ 10 ዓመታት ያህል በኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር በዋና ፀሀፊነት አገልግሏል፡፡ ካለፉት የተወሰኑ አመታት ጀምሮ ደግሞ ውጪ ከሚገኙ ወዳጆቹ እና ጓደኞቹ ጋር በመሆን አንድነት ኢነተርናሽናል ት/ቤትን ከፍተው በአመራርነት እየሰራ ይገኛል፡፡
  
  ደራሲ ሲሳይ ንጉሱ በ1991 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ስነ ጥበባት እና መገናኛ ብዙሃን ሽልማት ድርጅት በስነ ፅሁፍ ዘርፍ ተሸላሚ ነበር፡፡በወቅቱም 20 ሺ ብር፣ የክብር ዲፕሎማ እና የወርቅ ሜዳሊያ ተበርክቶለታል፡፡ በያዝነው አመትም በትምህርት አስተዳደር እና አመራር የማስተርስ ዲግሪውን አግኝቷል፡፡ ስለ ደራሲና መምህር ሲሳይ ንጉሱ እኔ ከአንደበቱ የሰማሁትን ይህን አካፈልኳችሁ ቀሪውን ደግሞ እናንተ ጨምሩበት……….

      ለትንሳኤ አባት ለሆነው ደራሲ ሲሳይ ንጉሱ እድሜ እና ጤና ተመኘሁ !!!!


No comments:

Post a Comment