Saturday, February 20, 2016

የአደዋ ማስታወሻ…!!!


አዲስ አበባ በዋና ከተማነት ከተቆረቆረችበት 1879. በተለይም 1880ዎቹ አጋማሽ ጀምሮ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና ማህበራዊ ማዕከል በመሆን በማገልገል ላይ ትገኛለች፡፡ ከተማዋ የምዕተ አመቱን ጉዞ የሚዘክሩ፣ ለተፈፀሙት ታሪካዊ ክንዋኔዎች ገላጭ እና አስረጂ የሆኑ ቅርሶችንም በውስጣ ይዛለች፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ በየጊዜው የተከናወኑ ታሪካዊ ድርጊቶችን እንዲሁም በታሪኩ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ያላቸውን ግለሰቦች ለማስታወስ የቆሙ ሀውልቶችም አሉ፡፡ ለመታሰቢያነት ከቆሙት ሀውልቶች አንዱ የሆነውን ለዛሬ በአጭሩ ለማየት እንሞክራለን፡፡  


በመዲናችን አዲስ አበባ ስላሉት ሀውልቶች ሲነሳ በቅድሚያ የሚጠቀሰው የቀድሞው አራዳ የአሁኑ ፒያሳ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ከአራዳ ጊዮርጊስ ፊት ለፊት የቆመው የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሀውልት ነው፡፡ በፀረ ኮሎኒያሊዝም ትግላቸው እና የዘመናዊ ስልጣኔን ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት ለሚታወቁት ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ማስታወሻ እንዲሆንላቸው ልጃቸው ንግስተ ነገስት ዘውዲቱ ያሰሩት ሀውልት ነው፡፡ የሀውልቱን ንድፍ ያዘጋጀው ጀርመናዊው አርክቴክት ሀርቴል/ሀርሴል/ ስፔንግለር ሲሆን የተሰራበት ቁሳቁስም ከነሀስ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

   
አፄ ምኒልክ የፊት ሁለት እግሮቹን ወደ ላይ አንስቶ የሚጋልብ ግዙፍ ፈረስ ላይ ተቀምጠዋል፡፡ በእጃቸው ጣምራ ጦር ይዘው ከራሳቸው ላይ ደግሞ ዘውድ ደፍተዋል፡፡ በጥሩ ሁኔታ እየተቀለበ እንደኖረ የሚያስታውቀው ፈረሳቸው ከእነ ሙሉ ጌጡ ይታያል፡፡ አባ ዳኛው እየተባለ የሚጠራው የአፄ ምኒልክ ፈረስ ፊቱን ወደ ሰሜን አድርጓል፡፡ ይህም ለመላው ጥቁር ህዝብ ኩራት የሆነውን ታሪክ ወደ አስመዘገበበት አድዋ ለማመላከት ነው፡፡ንግስት ዘውዲቱ ጀርመን ሀገር ድረስ ልከው በልዩ ትዕዛዝ የአባታቸው ማስታወሻ እንዲሆን ያሰሩትን ይህን ሀውልት በሀገራቸው ቆሞ ሳያዩት ነው በድንገት የሞቱት፡፡ ይሁንና የሀውልቱ ስራ ተጠናቆ ጥቅምት 22 /1923. ተመርቋል፡፡ በጣሊያን ወረራ ጊዜ አንዳንድ መረጃዎች ሙሉ በሙሉ ተነቅሎ እነዲቀበር ተደረጓል ሲሉ ሌሎች ደግሞ ተነቅሎ ተወስዷል ይላሉ፡፡ ያም ሆን ይህ በአርበኞች ተጋድሎ ጣሊያን ሀገሪቷን ከለቀቀ እና ነፃ ከወጣች በኋላ እንደገና ተጠግኖ እና ታድሶ መጀመሪያ በነበረበት ቦታ ላይ ሚያዚያ 27 /1934. ዳግም ተተክሏል፡፡ ከዚያም የአድዋ 100 አመት ሲከበር እድሳት ተደርጎለታል፡፡ ይህ ሀውልት ዛሬ ድረስ የኢትዮጵያን ህዝብ ታሪክ እና ጀግንነት የሚያስመሰክር ህያው ቅርስ ሆኖ ይገኛል፡፡
                                                          ክብር ለአድዋ ጀግኖቻችን እና ሰማዕታት…….

አትሌት ገንዘቤ ዲባባ በስፔን ካታላን በተደረገ የ3 ሺህ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር አሸነፈች።


  አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ይህን ውድድር ሁለተኛውን የዓለም ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ ነው ያሸነፈችው፡፡ አትሌቷ ይህንን ውጤት ያስመዘገበችው በአንድ ማይል የቤት ውስጥ ውድር የዓለምን ክበረ ወሰን ከሰበረች ከሁለት ቀን በኋላ ነው። ገንዘቤ ትናንት ምሽት በስፔን ካታላን በተካሄደው የ3 ሺህ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር ሁለት የአገሯን ልጆች አስከትላ ውድድሩን በበላይነት አጠናቃለች። ውድድሩን ለማጠናቀቅም 8 ደቂቃ ከ22 ሴኮንድ ከ50 ማይክሮ ሴኮንድ ፈጅቶባታል።
   ይህ ሰዓት በዓለም ሪከርድነት ካስመዘገበችው 8 ደቂቃ 16 ሰከንድ 60 ማክሮሰከንድ ቀጥሎ ሁለተኛው ፈጣን ሰዓት ነው። አትሌት ገለቴ ቡርቃ በ8 ደቂቃ 33 ሰከንድ 76 ማይክሮ ሰከንድ ሁለተኛ ስትሆን አትሌት ጎይቶም ገብረ ስላሴ ደግሞ ሶስተኛ ሆና አጠናቃለች።
  በ2015 በዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር  ''የዓለም ምርጥ ሴት አትሌት'' ትብላ የተሸለመችው ገንዘቤ የ2016 ውድድሯን የአንድ ማይል የዓለም  ክብር ወሰንን በመስበር ጀምራለች። ገንዘቤ እስካሁን ከሰበረቻቸው የዓለም ክብረወሰኖች አራቱ በቤት ውስጥ ውድድር ሲሆን አንድ ክብረወሰንም ከቤት ውጭ አሻሽላለች። ከብረወሰን ካስመዘገበችባቸው ውድድሮች ሶስቱን ያስመዘገበችው በስዊዲን መሆኑ ይታወቃል።

                                                 ምንጭ፦ ኢዜአ

Thursday, February 18, 2016

የጦር አርበኛ፣ ፀሐፊ- ተውኔት፣ ደራሲ፣ የመጀመሪያዋ ሴት የፓርላማ ተመራጭ እና ዲፕሎማት …… ወይዘሮ ስንዱ ገብሩ


    ወይዘሮ ስንዱ ገብሩ በሸዋ ክፍለ ሀገር በመናገሻ አውራጃ አዲስ ዓለም ከተማ ጥር 6 ቀን 1908 . ተወለዱ። አባታቸው ታዋቂው ዲፕሎማት፣ የመጀመሪያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል ፕሬዘደንት፤ ጣሊያኖች ከኢትዮጵያ ከወጡ በኋላ ደግሞ የምክር ቤቱ ፕሬዘደንት ፤በዳግማዊ ምኒልክ  ሹመትም የመጀመሪያው ጎንደር ከተማ አስተዳዳሪ የነበሩት ከንቲባ ገብሩ ደስታ ሲሆኑ ታናሽ እህታቸው ደግሞ የውብዳር ገብሩ (እማሆይ ጽጌ ማርያም) ናቸው።

 ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰበት ወቅት እቤታቸው አስተማሪ ተቀጥሮላቸው አማርኛ ትምህረት ከፊደል መቁጠር እስከ ዳዊት መድገም በቤታቸው ተማሩ። ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ሄደው ስዊድን ሚሲዮን ትምህርት ቤት በመግባት እስከ ስምንተኛ ክፍል ተምረዋል። ከንቲባ ገብሩ ወጣቷን ስንዱ ገብሩን እያስከተሉ ወደ ቤተ መንግሥትም ሆነ ሌላ ሥፍራዎች ይወስዷቸው እንደነበረና ከጊዜው አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንንም ጋር እንዳስተዋዋቋቸው ተዘግቧል።


    አልጋ ወራሹም የወጣቷን ብልህነትና ትጋት በማድነቅ ወደ ፈረንጅ አገር ተልከው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ ባዘዙት መሠረት ወይዘሮ ስንዱ 1921 . (ፊታውራሪ አመዴ 1919 . ይላሉ) ወደ ስዊስ ለትምህርት ቢሄዱም ኑሮው ስላልተመቻቸውና ትምህርት ይሰጥበት የነበረውን ጀርመንኛ ቋንቋ ስላልወደዱት ወደ ፈረንሳይ አቅንተው ትምህርታቸውን ቀጠሉ። በመጨረሻም ስዊስ እና ፈረንሳይ ሁለት ትምህርት ቤቶች በመዘዋወር በዲፕሎማ ተመረቁ። እዛው የሕግ ትምህርት ለመቀጠል ጀምረው የነበረ ቢሆንም፤ ፍላጎታቸው ወደ ሥነ-ጽሑፍ በማዘንበሉ በአጠቃላይ ለአምስት ዓመታት እዛው ተምረው ወደ ሀገራቸው ተመለሱ። ወደ ሀገራቸው እንደተመለሱም አዲስ አበባ በቅዱስ ጊዮርጊስ ትምህርት ቤት ውስጥ የፈረንሳይኛ ቋንቋን፣ ሀይጅን፣ ቁጥርንና የአማርኛ ድርሰት አጻጻፍን ማስተማር ጀመሩ።



     ፋሺስቶች ኢትዮጵያን በወረሩ ጊዜ ወይዘሮ ስንዱ   ሆለታ ውስጥ ከሚገኙ  የጦር መኮንኖች ጋር ተቀላቅለው ፋሺስቶችን ለመፋለም ወደ ቦሬ ሄዱ። እዚያም የመትረየስ አተኳኮስ ትምህርት ተማሩ። ወደ ነቀምት በመሄድም ሕዝቡን እየሰበሰቡ ስለ ነፃነት ማስተማሩን ተያያዙት። በዚህ ወቅት በባንዳዎች ጠቋሚነት በፋሽስት እጅ ከመውደቅ ለጥቂት አምልጠው ጎሬ ላይ ልዑል ራስ እምሩ ጦር ጋር ተቀላቀሉ። 

  ከዚያም በጦርነቱ የሚጎዱ አርበኞችን ለማከም የሚሆን ቀይ መስቀል ለማቋቋም መፈለጋቸውን ለራስ እምሩ አማክረው በተሰጣቸው አምስት መቶ ብር አቋቁመው አርበኞችን መርዳት ጀመሩ። ወዲያው ግን እርሳቸው ተቀላቅለውት የነበረው የጥቁር አንበሳ ጦር ሲመታ ጣልያን  ሠራዊት እጅ ተማርከው በእስር ወደ አዲስ አበባ አመጧቸውና የቁም እስረኛ ሆኑ።
የካቲት 12 ቀን 1929. ግራዚያኒ ለመግደል በተደረገው ሙከራ ወንድማቸው መሸሻ ገብሩ አሉበት በመባል ይታሰሱ ስለነበር ወንድማቸውን ከአደጋ ለማዳን ሲሞክሩ በድጋሚ በፋሺስቶች እጅ ወደቁ። በወቅቱ ግራዚያኒ ይኖርበት የነበረው ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ውስጥ ታሰሩ። ቀጥሎም ወደ አስመራ ከዚያ ወደ ምጽዋ ተወሰዱ። ከምጽዋ ወደብ ሦስት መቶ ወንዶችና ስምንት ሴቶች (እማሆይ ጽጌ ማርያምን ጭምር) ሆነው በመርከብአዚናራወደተባለች የኢጣሊያኖች እስር ቤት ተወስደው ዘጠኝ ወራት ታሰሩ። ከእስር በኋላም ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ በእንደዚህ ያለ ተግባር ላይ እንዳይሰማሩ ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ ቢሰጣቸውም፤ ማስፈራሪያው ሳይበግራቸው አርበኞችን በግጥም፣ በወኔ ቀስቃሽ ጽሑፎች በማበረታታት፣ መረጃ በማቀበል፣ መሣሪያ በማዳረስ የጀግንነት ተግባር ፈጽመዋል።

   ወ/ ስንዱ ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረችበት ወቅት በሀገር ፍቅር ስሜት በመነሣሣት በርካታ ስሜት ቀስቃሽ ግጥሞችን ጽፈዋል፡፡  የኢትዮጵያ ትግል፣ አድዋ፣ አፄ ቴዎድሮስ፣ የታጋዮች ስሜት ከግራዚያኒ ንግግር በኋላ፣ ኮከብህ ያውና ያበራል ገና፣ የየካቲት ቀኞች፣ ከማይጨው መልስ፣ የኑሮ ስህተት፣ የልቤ መጽሐፍየታደለች ሕልም፣ ርዕስ የሌለው ትዳር፣ ፊታውራሪ ረታ አዳሙየሚሉት ሥራዎቻቸው የገጣሚዋን የሀገር ፍቅር ስሜትና የሥነ ጽሑፍ ችሎታ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ 
  ከድል በኋላ ወይዘሮ ስንዱ  ለሁለት ዓመታት ደሴ ከተማ የሚገኘው ወይዘሮ ስሂን ትምህርት ቤት አስተዳዳሪ በመሆን፣ በኋላም ወደ አዲስ አበባ ተመልሰው እቴጌ መነን ትምህርት ቤት ምክትል ርዕሰ መምህርነት፣ ከዚያም የመጀመሪያዋ ሴት ርዕሰ መምህር ሆነው አገልግለዋል። 1948 . እስከ 1952. ድረስ የመጀመሪያዋ የሴት የሕግ መምሪያ ምክር ቤት  አባልና  የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ሊቀ መንበር ሆነውም አገልግለዋል። በዚህ ምክር ቤት አባል በነበሩበት ጊዜ ብቸኛዋ ሴት ከመሆናቸውም ባሻገር የሴቶች እኩልነት በማይከበርበት ጊዜ እናየወንድ ዓለምበገነነበት የታሪክ ምዕራፍ የሴቶችን ሰብዓዊ መብት ለማስከበርና እኩልነትን በሕግ ለማስተማመን ብዙ የታገሉ ሴት ነበሩ።



    የኢትዮጵያ ቀይ መስቀልና ቀይ ጨረቃ ማኅበር ፕሬዝዳንት፣ የሕዝባዊ ኑሮ እድገት ዋና ፀሐፊነትና አስተዳዳሪነት፣ በምዕራብ ጀርመን ለሦስት ዓመት የትምህርት አታሼ በመሆን አገልግለዋል። ወይዘሮ ስንዱ ገብሩ ላበረከቷቸው አስተዋጽዖዎች የወርቅ ሜዳሊያ፣ የንግሥት ሣባ የወርቅ ኒሻን፣ የቀይ መስቀል የወርቅ ሜዳሊያ እና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ተሰጥቷቸዋል።



   የመጀመሪያዋ የሴት ፓርላማ አባል፣ የሴት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች፣ ጀግናና ፀረ-ፋሺስት አርበኛ፣ ፀሐፊ ተውኔት፣ የመጽሐፍ ደራሲ፣ እና የመጀመሪያዋ የሴት ዲፕሎማት ስንዱ ገብሩ(የክቡርት ዶክተር) ሰኞ ሚያዝያ 12 ቀን 2001 . በተወለዱ በ93 ዓመታቸው ሕይወታቸው አልፎ መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተቀብረዋል።