Saturday, November 28, 2015

ከሜጋ ትያትር እስከ ኮራ እና አፍሪማ ተሸላሚነት …….. አርቲስት ፀደንያ ገብረማርቆስ


   “ገዴ” እና “ቢሰጠኝ” የተሰኙ ሁለት አልበሞች አሏት፡፡ እ.ኤ.አ በ2004 “እወድሃለሁ” በሚለው ስራዋ የኮራ ሙዚክ አዋርድ ተሸላሚ ናት፡፡ በቅርቡ ደግሞ በናይጄሪያ ሎጎስ በተካሄደው ኦል አፍሪካ ሙዚክ አዋርድስ /አፍሪማ/ በምስራቅ አፍሪካ ምርጥ የሴት ድምፃውያን ምድብ አሸናፊ ሆናለች፡፡ ለተለያዩ ፊልም እና ድራማዎች ሳውንድ ትራክ /ማጀቢያ ሙዚቃ/ ሰርታለች፡፡ ቀደም ሲል በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 በሚቀርበው የ “አይሬ” ፕሮግራም ትሰራ የነበረ ሲሆን አሁን ደግሞ በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 “ዜማ ፍቅር” የተሰኘ ፕሮግራምን ታቀርባለች፡፡ ሶስተኛ አልበሟንም ሰርታ አጠናቃለች፤ አርቲስት ፀደንያ ገብረማርቆስ፡፡
   አርቲስት ፀደንያ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ልዩ ልዩ ሽልማቶችን አግኝታለች፡፡ በኮራ እና በአፍሪማ አራት ጊዜ ተወዳድራ ፣ ሶስት ጊዜ ለእጩነት ቀርባ በሁለቱ አሸንፋለች፡፡ እ.ኤ.አ በ2004 ከኬንያዊቷ አቺንግ አቦራ ጋር “እወድሃለሁ” በተሰኘው ስራዋ በምስራቅ አፍሪካ ምርጥ የሴት ድምፃዊት ተብላ የሽልማቱ ተጋሪ ሆናለች፡፡ ዘንድሮ ደግሞ በ2015 ለሀርየት ፊልም ማጀቢያ በሰራችው “የት ብዬ” ዘፈን  በ24 ካራት ወርቅ የተለበጠ የአፍሪማን የዋንጫ ሽልማት አግኝታለች፡፡ በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 የለዛ ፕሮግራም የአመቱ የአድማጮች ምርጥ የፊልም ማጀቢያ በሚል “የት ብዬ” በተሰኘው ዘፈን አሸናፊ ሆናለች፡፡


  በቀድሞው ደብረ ያሬድ (ሜጋ ትያትርም) ለተወሰኑ አመታት ሰርታለች፡፡ በእንግሊዘኛ ዘፈኖች ሙዚቃን አሀዱ ያለችው አርቲስት ፀደንያ ገብረማርቆስ ቀስ በቀስ ወደ አማርኛ ስራዎች በማምራት ሁለት ያህል አልበሞችን እና በርከት ያሉ ነጠላ ዜማዎችን ለአድናቂዎቿ አድርሳለች፡፡ “ገዴ” የተሰኘው የመጀመሪያ አልበሟ በኬንያዊው አቀናባሪ ዴቪድ ኦቴኖ የተሰራ ሲሆን አምባሰል ሙዚቃ ቤት ነው የታተመው፡፡ “ቢሰጠኝ” የተሰኘው አልበሟ ደግሞ ጥበቡ ወርቅዬ ኢንተርቴይመንት የታተመ ሲሆን ቅንብሩን ዳግማዊ አሊ ሰርቶታል፡፡


   አሁን ደግሞ ሶስተኛ አልበሟን አጠናቃ ለአድናቂዎቿ ለማድረስ ጉድ ጉድ እያለች ትገኛለች፡፡ የዚህ አልበም በዛ ያሉት ግጥሞች የይልማ ገብረአብ ሲሆኑ ጌትነት እንየው፣ አብዲራዋ (የህመሜ ደራሲ) እና ፋሲል ከበደ ተሳትፈዋል፡፡ አብዛኛዎቹን ዜማዎች እሷ እራሷ ናት የሰራቻቸው፡፡ ቅንብሩን ደግሞ አቤል ጳውሎስ፡፡ ሙዚቃ ስትጀምር አማርኛ እንዳትዘፍን የተባለችው ይህቺ ድምፃዊት የሀገሯን ሙዚቃ በአለም መድረክ እያስተዋወቀች ትገኛለች፡፡ በዚህም በርካታ ሽልማቶችን ተጎናፅፋለች፡፡


  እ.ኤ.አ በ2003 ከግርማ ይፍራሸዋ ጋር የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራትን በመዘዋወር ስራዎቿን አቅርባለች፡፡ በ2009ም በወርልድ ሙዚክ ከእነ ፈለቀ ሀይሉ (ሳክስፎን) ፣ ሳሙኤል ይርጋ (ፒያኒስት) ፣ ተራማጅ ወረታው (ማሲንቆ) እንዲሁም ስንታየሁ ዘነበ እና እሷ ሆነው ሁለት አልበሞችን ሰርተው በአለም አቀፍ ፌስቲቫሎች ላይ ተሳትፈዋል፡፡
   

  ከኤዘር ኦርኬስትራ ጋርም አልያንስ - ኢትዮ ፍራንሲስ ከውጪ በመጡ የሙዚቃ ባለሙያዎች ታጅባ “ባቲ” የተሰኘ ስራዋን አቅርባለች፡፡ ከዚያም በኋላ ከጋሽ መሀሙድ አህመድ ጋር በፈረንሳይ ሀገር ዝግጅቶቿን አሳይታለች፡፡ ድምፃዊት ፀደንያ ገብረማርቆስ ከድምፃዊነት፣ ዜማ ደራሲነት እና ፕሮግራም አቅራቢነት ባሻገር ቀደም ብላ ማስታወቂያዎችንም ትሰራ ነበር፡፡ ለአብነትም አብወለድ ፣ ገርልጊ ፣ ካዲስኮ እና ሌሎችንም መጥቀስ ይቻላል፡፡

  ትውልዷ እና እድገቷ እዚሁ መዲናችን አዲስ አበባ የሆነው ፀደንያ የመንታ ወንድ ልጆች እናት ናት ፡፡ ቀሪ ዘመኗም የስኬት እና ብልፅግና እንዲሆን በመመኘት እኔ ፅሁፌን በዚሁ ላብቃ ሌላውን እናንተ ጨምሩበት ……

Wednesday, November 4, 2015

በስለት ተወልዶ በስስት ያደገው …… ድምፃዊ ኪሮስ አለማየሁ


  በስለት ተወልዶ በስስት እንዳደገ ይነገርለታል፡፡ 1944. ትግራይ ክልል ፀአዳ አምባ ወረዳ ሰንደዳ ቀበሌ ነው የተወለደው ድምፃዊ ኪሮስ አለማየሁ፡፡ የቤተ ክህነት እውቀትን የቀሰመው ኪሮስ የአንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በፍሬወይኒ ውቅሮ እና አፄ ዮሀንስ /ቤቶች ተከታትሏል፡፡ በመምህርነት እና በሀላፊነትም ሰርቷል፡፡ ከዚያም ከትግራይ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ በራስ ትያትር ለአምስት አመታት ያህል የትግርኛ ሙዚቃዎችን ተጫውቷል፡፡ የመጀመሪያ አልበሙንም ራስ ትያትር እያለ ከሸበሌ ባንድ ጋር በመሆን ለአድናቂዎቹ አድርሷል፡፡
   

   1970ዎቹ አጋማሽ  በአዲስ  አበባ  ማዕከላዊ  እስር  ቤት  ታስሮ  የነበረው  ኪሮስ  አለማየሁ  በኪነቱ  ውስጥ  በነበረው  ቆይታ  በርከት  ያሉ  አስደሳች  አሳዛኝ እና አስቂኝ  ነገሮችን አሳልፏል፡፡ በስራዎቹም  ለትግሪኛ  ሙዚቃ  እድገት  ከፍተኛ  አስተዋፅኦ  አድርጓል፡፡ በተለያዩ   ርዕሰ  ጉዳዮች  ላይ  ያቀነቀነው  አንጋፋው  ድምፃዊ  ግጥም እና ዜማ  ይደርሳል፤ ዋሽንት  እና ክራር  የመሳሰሉትን  የሙዚቃ  መሳሪያዎችም  ይጫወታል፡፡

  
ድምፃዊ ኪሮስ አለማየሁ ነገሮችን እና ሁኔታዎችን አይቶ የመድረስ እና ከዜማ ጋር አዋህዶ የመጫወት ተሰጥኦው ላቅ ያለ ነው ይባልለታል፡፡ በአንድ ወቅትም ባለቤቱ አዲስ ሙሽራ ሆና ስትስቅ ስትጫወት እሷን በማየትአይቁንጅናየተሰኘውን ስራ እንደሰራው እና ከዚያም 1983. በካሴት እንዳሳተመው ይነገራል፡፡


ድምፃዊ ኪሮስ አለማየሁ በግሉ አምስት ከሌሎች ድምፃውያን ጋር ደግሞ ሁለት ያህል አልበሞችን ሰርቷል፡፡ ድምፃዊው በጥቅምት ወር 1986. ከዚህ አለም በሞት ተለይቷል፡፡ በስሙ ቤተ መፅሃፍት የተቋቋመለት ሲሆን ከመቀሌ ዩኒቨርስቲም የክብር ዶክትሬትን አግኝቷል፡፡ በቅርቡም የህይወት ታሪኩን በተመለከተ መፅሃፍ ተፅፎለታል፡፡ እሱ በህይወት ባይኖርም ስራዎቹ ህያው ናቸው እና ሁሌም ሲታወስ ይኖራል፡፡

Monday, November 2, 2015

ልክ በዛሬዋ ቀን ጥቅምት 22 ቀን 1923 ዓ.ም ነበር የአፄ ምኒልክ ሐውልት የተመረቀው፡፡

  
   አዲስ አበባ ከተቆረቆረች ወዲህ በውስጧ ከቆሙት ሐውልቶች በቅድሚያ ከሚጠቀሱት አንዱ የአፄ ምኒልክ ሐውልት ነው፡፡ ሐውልቱን ያሠሩት ንግሥት ዘውዲቱ ሲሆኑ የቆመው የአባታቸው የአፄ ምኒልክ ማስታወሻ እንዲሆን ታስቦ ነው፡፡ የሐውልቱን ንድፍ ያወጣው ጀርመናዊ አርክቴክት ሀርቴል ስፔንግለር ነበር፡፡ ሐውልቱም የተቀረፀው ጀርመን ሀገር ሲሆን የተሰራውም ከነሐስ ነው፡፡ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሀገር በማቅናቱና በፀረ ኢምፔሪያሊስት ትግላቸው የታወቁ ንጉሥ ነበሩ፡፡ ሐውልቱም ይህን ታሪካዊ ውሎአቸውን የሚያንፀባርቅ ሆኖ የተቀረፀ ነው፡፡ በሐውልቱ ላይ አፄ ምኒልክ ካባ እንደለበሱ አንባር አጥልቀው በእጃቸው ጣምራ ጦር ይዘው በፈረሳቸውበአባ ዳኘውላይ ተቀምጠው በግርማ ሞገስ ይታያሉ፡፡ የሐውልቱ ቁመት ከተፈጥሮ አካላዊ መጠን በላይ ሲሆንአባ ዳኘውፊቱን ወደ ሰሜን መልሶ በኋላ እግሮቹ ቆሞ፣ የፊት እግሮቹን ወደላይ አንስቶ ይታያል፡፡


  ሐውልቱ ከጀርመን ሃገር ተሠርቶ ከመጣ ወዲህ የሚቆምበት ቦታ በዝግጅት ላይ እያለ ንግሥት ዘውደቱ በድንገት መጋቢት 22 ቀን 1922 . አረፉ፡፡ ነገር ግን የተጀመረውን ሥራ የንግሥቲቱን አልጋ የወረሱት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ እንዲጠናቀቅ በማድረግ በንግሥናቸው በዓል ዋዜማ ጥቅምት 22 ቀን 1923 . በታላቅ ክብር በንጉሠ ነገሥቱ ተገለጠ፡፡ ስድስት ቀን የፈጀው የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የንግሥና በዓል የተጀመረው በአፄ ምኒልክ ሐውልት ምረቃ ሲሆን፣ በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ ከተገኙት፣ እንግዶች አንዱ የነበረው ኢቨሊን ዋህግ ሥነ ሥርዓቱን አስመልክቶ በአንድ  መጽሐፉ ውስጥ እንደሚከተለው ገልፆታል፡፡የሃገር ተወላጅ የሙዚቃ ባንድም ሙዚቃ ያሰማ ጀመር፡፡ በአውቶሞቢል ንጉሡ መጡ፡፡ ... ንግግርም ካደረጉ በኋላ ገመዱን ስበው ሐውልቱ የተሸፈነበትን አረንጓዴውን ሐር ገለጡ፡፡ ከሐውልቱም ግርጌ ዘመን የማይሽረው ጥቅስ የተቀረፀ ሲሆን እንዲህም ይነበባል፡-

 ከትልቅ ወይም ከትንሽ ቢሆን መወለድ ሙያ አይደለም ራስን ለታላቅ ታሪክ መውለድ ግን ሙያ ነው፡፡


  1928 . ጣሊያን ኢትዮጵያን ወርሮ አዲስ አበባን ከያዘ በኋላ ቤኔቶ ሙሶሊኒ በፋሽስት ፖሊሲው መሠረት ማንኛውም የኢትዮጵያን ነፃነት የሚያንፀባርቅ ማስታወሻ ለማስወገድ በተንቀሳቀሰበት ጊዜ የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሐውልት የአድዋ ጦርነት ማስታወሻና የጣሊያኖች ሽንፈት ምልክት ስለነበር በዚሁ የፋሽስቶች ዘመቻ ዒላማ ውስጥ ገባ፡፡ ማርሻል ባዶልዮ አዲስ አበባ እንደገባ ሙሶሊኒ ከሮም ባስተላለፈለት መልዕክት የአፄ ምኒልክን ሐውልት እንዲያፈርስ አሳስቦት ነበር፡፡ ሆኖም ግን ባዶሊዮ ትዕዛዙን ከማስፈፀሙ በፊት በግራዚያኒ ስለተተካ የማፍረሱ ሥራ ለተወሰነ ጊዜ ዘገየ፡፡ ሙሶሎኒ ጊዜ ሳያጠፋ በቅኝ ግዛት ሚኒስትር በነበረው በሌሶና በኩል ለግራዚያኒ የሚከተለውን ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡

  የምኒልክና የይሁዳ አንበሳ ሐውልቶች በሃያ አራት ሰዓት እንዲፈርሱግራዚያኒም ምንም እንኳን ሐውልቶች ከግዙፍነታቸው የተነሣ ለማፍረስ የቴክኒካል ችግር ቢኖርም በትዕዛዙ መሠረት እንደሚፈፀም ያረጋግጣል፡፡ ነገር ግን የማፍረሱ ሥራ የጣሊያኑ የቅኝ ግዛት ሚኒስትር ሌሶና እና የሥራ ሚኒስትሩ ችቦሊ ጊገሊ ባሉበት እንዲፈፀም ስለተወሰነ ለብዙ ወራት ዘግይቶ ባለሥልጣኖቹ በተገኙበት የማፍረሱ ሥራ ማታ ጥቅምት 16 ተጀምሮ ንጋቱ ላይ 17/1936 .. ተጠናቀቀ፡፡ ብርሃኑ ድንቄየአምስቱ የመከራ ዓመታት አጭር ታሪክበሚለው መጽሐፋቸው ጣሊያኖች የአፄ ምኒልክን ሐውልት እንዴት እንዳፈረሱት እንደሚከተለው ገልፀውታል፡፡

  በቅድሚያ ሐውልቱ ያለበትን አካባቢ ረጅም እንጨት እየማገሩ በቆርቆሮ ሲያጥሩ ሰነበቱ፡፡ ይህንን ያየው የአዲስ አበባ ሕዝብ ሊያፈርሱት ነው ብሎ እርስ በእርሱ በሐዘን መነጋገሩን ቢሰሙልናድስነው ብለው አስወሩ፡፡ ሁሉንም ነገር ካመቻቹ በኋላ ግን በየበሩ ጥበቃውን አጠናክረው ... ወደ ማታ የአራዳን አካባቢ በታንክ አጥረው በባውዛ ሌሊቱን ከተማውን እየተቆጣጠሩ በሌላ ኃይል ደግሞ ሐውልቱን ሲያፈርሱ አድረው ሲነጋጋ ወደ አልታወቀ ቦታ ወስደው ቀበሩት፡፡ ሕዝቡ እድሜና ፆታ ሳያግደው ሐዘኑን ይገልጽ እንደነበር አዛውንቶች ይመሰክራሉ፡፡ በጊዜው የአዲስ አበባ ነዋሪ የነበረው የሃንጋሪው ዶክተር ላዲ ስላስ ላቫ እንደፃፈው ሐውልቱ ከፈረሰበት ቦታ ቆመው ያለቅሱ የነበሩትን ሰዎች የጣሊያን ወታደሮች በኃይል ይበትኑ እንደነበር ገልፆአል፡፡ በሌላ ዘገባ ደግሞ አንድ ሕፃን ልጅ ሲያለቅስ ጣሊያኖች ደርሰው ለምን እንደሚያለቅስ ቢጠይቁትየንጉሱን ምልክት ስላወረዳችሁ ነውብሎ እንደመለሰላቸውና ጣሊያኖችም ከሙሶሊኒ ሌላ ንጉሥ እንደሌለው በመንገር ልጁን ገርፈው እንዳባረሩት ተገልጿል፡፡


   ጣሊያኖች የኢትዮጵያ ነፃነት ምልክት የሆኑትን ሐውልቶች በማፈራረስ ግማሾቹንም ወደ ጣሊያን አግዞ በመውሰድ የኢትዮጵያዊያንን የነፃነት መንፈስ ለመስበርና የጣሊያንን የበላይነት በሕዝቡ መሀል ለማስረፅ ይታገሉለት የነበረው ዓላማ ሳይሳካ ቀረ፡፡ በመጨረሻም በአርበኞች ትግልና በእንግሊዞች እርዳታ ተሸንፈው ሀገር ለቀው ወጡ፡፡ ከነፃነት በኋላም የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሐውልት ከተቀበረበት ቦታ ወጥቶ እንደገና ታድሶና ተጠግኖ ቀድሞ በነበረበት ቦታ ሚያዝያ 27 ቀን 1934 . እንዲቆም ተደረገ፡፡ 1988 . የአድዋ ድል መቶኛ ዓመት ሲከበር ሐውልቱ ጥገና የተደረገለት ሲሆን በአሁኑ ጊዜ በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡