Thursday, June 5, 2014

በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የማተሚያ ማሽን መገጣጠሚያ ፋብሪካ ስራ ጀመረ

 

ጣና ኮሙኒኬሽንስ ከሳምሰንግ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ጋር በመተባበር በባህር ዳር በሀገሪቱ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የማተሚያ ማሽን መገጣጠሚያ ፋብሪካ አቋቁመዋል፡፡ጥረት በተሰኘ ሀገር በቀል ኩባንያ ስር የተቋቋመው የማተሚያ ማሽን መገጣጠሚያ ፋብሪካው መከፈት የኢትዮጰያ መንግስት ከሳምሰንግ የኤሌክትሮኒክስ ጋር ባለፈው አመት ሰኔ ወር ላይ ያደረገው የቴክኖሎጂ ሽግግርና የትብብር ስምምነት አንዱ እርምጃ ነው ተብሏል፡፡
 በስምምነቱም መሰረት ሳምሰንግ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ከጣና ኮሙኒኬሽንስ ጋር በመተባበር ባለከለር ሌዘር ጀት ፕሪንተርን ጨምሮ የተለያዩ አይነት ሞዴል ያላቸው ፕሪንተሮችን በመገጣጠም በቅርቡ ለገበያ ያቀርባል፡፡ ፋብሪካው በቀን 70 ፕሪንተሮችን በመገጣጠም ላይ ሲሆን ለ200 ኢትዮጵያዊ ሰራተኞችም የስራ እድል ፈጥሯል፡፡ የጥረት ኩባንያ ዋና ስራስኪያጅ አቶ ታደሰ ካሳ እንዳሉት ድርጅቱ ከስራ እድል ፈጠራውም ባሻገር በቴክኖሎጂ ሽግግርም የሚያበረክተው አስተዋፅኦ የላቀ ነው፡፡
  ጣና የማተሚያ ማሽን መገጣጠሚያ ኩባንያ በቀጣይም ምርቱን በማስፋት ከ700 በላይ የሰው ሀይል ለመቅጠር እቅድ ይዟል፡፡ሳምሰንግ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ በተመሳሳይ እንደ ልብስ ማጠቢያ ማሽንና የኤሌክትሪክ ምድጃ ያሉ የቤት ውስጥ የኤሌክትሪክ መገልገያዎች ማምረቻ በደብረ ብርሀን ከተማ ለመክፈት እቅድ እንዳለውም ለማወቅ ተችሏል፡፡
  የኢትዮጵያ መንግስት በቀጣይ ከኤሌክትሮኒክስ ኩባንያው ጋር በትምህርትና ለገጠር መንደሮች ዘመናዊ የመገናኛ ቴክኖሎጂዎችን ለመስራት ስምምነት ላይ መድረሳቸው ይታወሳል፡፡

No comments:

Post a Comment