Tuesday, May 27, 2014

"ባላገሩ" ኢትዮጵያዊው የሰላም ተጓዥ ከአዲስ አበባ ወደ ባህር ዳር የእግር ጉዞ ጀመረ


  ኢትዮጵያዊው የሰላም ተጓዥ ከድር አሰፋ "ባላገሩ" በ18/9/2006 ማለዳ ከአዲስ አበባ በመነሳት ወደ ባህር ዳር ከተማ የሚያደርገውን የእግር ጉዞ ጀመረ። "ባላገሩ በሀገሩ ይኑር፣ አገር አለኝ ወገን አለኝ"  የሚል መሪ ቃል አንግቦ ሰኞ ማለዳ ላይ አዲስ አበባ ጎተራ አካባቢ ከሚገኘው የብሄር ብሄረሰቦች አደባባይ መነሻውን አድርጓል።
  ጉዞውን የሚያደርገው ሞፈርና ቀንበር ተሸክሞ የጡሩንባ ድምፅ እያሰማ ሲሆን ይህንን ማድረጉ ደግሞ መጪው ጊዜ የስራ በመሆኑ በተለይ አርሶ አደሩ ለልማት እንዲነሳሳ ለማድረግ መሆኑን ገልጿል። ጉዞውን ለማድረግ ያነሳሳው  ወደ አገራቸው ተመልሰው እየሰሩ የሚገኙትን ኢትዮጵያዊያን ለማበረታታት እንዲሁም በህገ ወጥ መንገድ አገራቸውን ለቀው የሚወጡ እዚሁ ሰርተው መለወጥ እንደሚችሉ መልእክት ለማስተላለፍ መሆኑን ተናግሯል።
   የአሁኑም ጉዞ መታሰቢያነቱ በህገ ወጥ ዝውውር ምክንያት በየበረሃው ህይወታቸውን ላጡ ኢትዮጵያዊያን  ነው ብሏል፡፡ ፈታኙን የእግር ጉዞ በስኬት በማጠናቀቅ ምንም ነገር ማድረግ እንደሚቻል ለኢትዮጵያዊያን ማሳየት አለብኝ የሚለው ባላገሩ ባህር ዳር ለመግባት 16 ቀን ሊፈጅበት እንደሚችልም ገምቷል። "ባላገሩ" ከአዲስ አበባ በመነሳት ረጅሙን ጉዞ በማጠናቀቅ ባህር ዳር እስከሚገባ ድረስ አላማውን የሚደግፉ ሁሉ ከጎኑ በመሆን ውሃ በማቀበልና በማበረታታት እንደሚያግዙትም ተስፋ አድርጓል።
                                                  ምንጭ:- ኢዜአ

No comments:

Post a Comment