Sunday, September 21, 2014

ጥቂት ስለ “ባንክ ኦፍ አቢሲኒያ /አቢሲኒያ ባንክ/ ”

  
  ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ባንክ የተቋቋመው በ1897ዓ.ም ሲሆን “ባንክ ኦፍ አቢሲኒያ” ይባል ነበር፡፡ ባንኩንም በበላይነት ይቆጣጠርና ይመራው የነበረው በወቅቱ የእንግሊዛውያን ንብረት የነበረው የግብፅ ብሄራዊ ባንክ እንደነበር ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ ባንክ ኦፍ አቢሲኒያ የራስ መኮንን ይዞታ በነበረው የዛሬው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሰቲ /6ኪሎ ካምፓስ/ ቅጥር ግቢ ውስጥ ነው፡፡ባንኩም በወቅቱ ከነበሩት የሳር ክዳን ቤቶች ውስጥ በአንዱ ተቋቋመ፡፡


  በእንግሊዞች የበላይ ገዥነትና ንብረትነት የተቋቋመው ይህ ባንክ እስከ 1923ዓ.ም ድረስ በዚሁ ስም አገልግሎቱን ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ሚያዚያ 23 ቀን 1924ዓ.ም አፄ ኃይለስላሴ ባንኩን ከእንግሊዝ ማህበር ላይ በስምምነት ገዝተው፣ ይህንንም በህግ አሳወቀው የኢትዮጵያ መንግስት ባንክ ተብሎ እንዲሰየም አደረጉ፡፡ በዚህም ምክንያት ባንኩ በአፍሪካውያን ንብረትነት በአፍሪካ ውስጥ የተመሰረተ የመጀመሪያው ባንክ (African Indigenous Bank) ለመሆን በቅቷል፡፡ በታህሳስ ወር 1956ዓ.ም የኢትዮጵያ መንግስት ባንክ በሚል መጠሪያ ይታወቅ የነበረው ይህ ባንክ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በመባል ለሁለት ተከፈለ፡፡

  አሁን የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በሚል ስያሜ የሚታወቀው ባንክ የተቋቋመው ግንቦት 23ቀን 1901ዓ.ም ነበር፡፡ ይህ ባንክ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ የስያሜ ለውጦች አድርጓል፡፡ እነሱም፡-
         ከ1901 – 1928ዓ.ም የእርሻ እና የንግድ ማስፋፊያ የኢትዮጵያ ማህበር
         ከ1937 – 1942ዓ.ም የኢትዮጵያ የእርሻ ባንክ
         ከ1942 – 1943ዓ.ም የኢትዮጵያ የእርሻ እና ንግድ ባንክ
         ከ1943 – 1962ዓ.ም የኢትዮጵያ ልማት ባንክ
         ከ1962 – 1971ዓ.ም የእርሻ እና ኢንዱስትሪ ልማት ባንክ አክሲዮን ማህበር
         ከ1971 – 1987ዓ.ም የእርሻ እና ኢንዱስትሪ ልማት ባንክ
         ከ1987ዓ.ም ወዲህ የኢትጵያ ልማት ባንክ በመባል ይታወቃል፡፡
                                                        
                                              ምንጭ ፡- ህብር ኢትጵያ

No comments:

Post a Comment