Monday, March 9, 2015

ኢትዮጵያ ሻምፒዮናውን ሶስተኛ ሆና አጠናቀቀች


    ኢትዮጵያ ያዘጋጀችውን 12ኛውን የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሶስተኛ ሆና አጠናቀቀች፡፡ ናይጀሪያ እና ደቡብ አፍሪካ 1ኛ እና 2ኛ በመሆን የሻምፒዮናውን ንግስና ደፍተዋል፡፡
    ኢትዮጵያ 6 ወርቅ፤ 12 ብር እና 10 ነሐስ በድምሩ 28 ሜዳሊያ በማግኘት ነው ውድድሯን በሶስተኝነት ያጠናቀቀችው፡፡ ኢትዮጵያ በሰበሰበችው ሜዳሊያ ብዛት ቀዳሚ ሆናለች፡፡ ኢትዮጵያ ከሰበሰበቻቸው 6 የወርቅ ሜዳሊያዎች 5ቱ በሴቶች የተገኙ ናቸው፡፡ ዮሚፍ ቀጀልቻ በወንዶች 5 ሺህ ሜትር ለሀገሩ ብቸኛውን በወንዶች የተገኘ ወርቅ አስመዝግቧል፡፡
      ኢትዮጵያ በዘውዴ ማሞ 3 ሺህ ሜትር መሰናክል ሴቶች፤ በእታገኝ ማሞ 5ሺህ ሜትር ሴቶች፤ በኋላየ በለጠ 5ሺህ ሴቶች የዕርምጃ ውድድር በንጉሴ ብረስ በ3ሺህ ሜትር ሴቶች እንዲሁም በዳዊት ስዩም 1ሺህ 5 መቶ ሜትር ሴቶች አማካኝነት ወርቅ ማግኘት ችላለች፡፡ ኢትዮጵያ ከ2 ዓመት በፊት በሞሪሸየስ ተካሂዶ በነበረው 11ኛው የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና 22 ሜዳሊያ በማግኘት በተመሳሳይ ሶስተኛ ደረጃ ሆና ማጠናቀቋ ይታወሳል፡፡  ከተገኘው 7 የወርቅ ሜዳሊያ 6ቱ በሴቶች የተገኘ ነበር፡፡
      በዚህ ውድድር ናይጀሪያ 12 ወርቅ፤ 8 ብር እና 7 ነሐስ በማግኘት የውድድሩ ፈርጥ ሆናለች፡፡ ናይጀሪያዎች በአጭር ርቀት ውድድሮች ያሳዩት ብቃት ለበላይነት አብቅቷቸዋል፡፡
     ደቡብ አፍሪካ በበኩሏ 9 ወርቅ፤ 7ብር እና 7 ነሐስ በማግኘት በሻምፒዮናው ሁለተኛ ቦታን ተቆናጣለች፡፡ ሁለቱ ሀገራት በ11ኛው የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮናም ተመሳሳይ ውጤት ይዘው ማጠናቀቃቸው ይታወሳል፡፡
       ግብፅ እና ኬኒያ በቀደም ተከተል 4ኛ እና 5ኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ በውድድሩ ከተሳተፉት 37 ሀገራት 18ቱ በሜዳሊያ ሰንጠረዥ ገብተዋል፡፡ ውድድሩን 6ኛ ሆና ያጠናቀቀችው አልጄሪያ 13ኛውን የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለማዘጋጀት መሰናዶውን ከኢትዮጵያ ተረክባለች፡፡ ኢትዮጵያ የተሳካ መሰናዶ ማድረጓን ከተሳታፊዎች እና ዝግጅቱን ከሚመሩት አካላት ተመስክሮላታል፡፡                                                                                       ምንጭ ፡- ኢ.ብ.ኮ  

No comments:

Post a Comment