Monday, March 30, 2015

የክቡር ዶክተር አሊ ቢራ የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ተከበረ፡፡


   በኦሮሚኛ ሙዚቃው የሚታወቀው እና በዚሁ ዘርፍ ግማሽ ክፍለ ዘመንን ያስቆጠረው ክቡር ዶክተር አሊ ቢራ የወርቅ ኢዮ ቤልዩ በዓሉን በደመቀ ሁኔታ አክብሯል፡፡ ይህንን ምክንያት በማድረግም ላበረከተው አስተዋፅኦ በአዳማ ከተማ የምስጋና ስነ ስርዓት ተዘጋጅቶለት ነበር፡፡ በዚሁ ስነ ስርዓት ላይ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ፣ የተለያዩ ድምፃውያን ፣ የአርቲስቱ አድናቂዎች እና ወዳጅ ዘመዶቹ ተገኝተዋል፡፡ በወቅቱም በድምሩ 5 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ የመኪና እና የመኖሪያ ቤት ስጦታ ከኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ተበርክቶለታል፡፡ በመድረኩ ላይም ድምፃዊ ቀመር የሱፍ እና ታደለ ገመቹ የእሱን ስራዎች ተጫውተዋል፡፡

   ስምንት ያህል ቋንቋዎችን የሚናገረው አሊ ቢራ በድሬዳዋ ከተማ ነው የተወለደው፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በድሬድዋ ከተማ በመድረስ ጀዲድ እና በልዑል ራስ መኮንን ት/ቤት እንዲሁም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በአዲስ አበባ ካቴዴራል ተከታትሏል፡፡ በኋላም በካሊፎርኒያ ሳንታሞኒካ ት/ቤትም በሙዚቃ ትምህርት ዘርፍ የከፍተኛ ትምህርቱን መማር ችሏል፡፡ 

  ሶስት በአሊ ስም የሚጠሩ ታዳጊዎች በነበሩበት የአፈረን ቀሎ የሙዚቃ እና የባህል ቡድን 14 ዓመቱ መሳተፍ የጀመረው የያኔው ታዳጊ ከቀሪዎቹ እንዲለይ በማለት ጓደኞቹ አሊ ቢራ በማለት መጥራት ጀመሩ፡፡ ቢራ የሚለው ስያሜ ለመጀመሪያ ጊዜ መድረክ ላይ ከተጫወተውብራዳ ብርሄ /Birraadahaa Barihee/” የመጣ እንደሆነ ይነገራል፡፡ቤተሰቦቹ ያወጡለት ስም ግን አሊ መሀመድ ሙሳ ነው፡፡ አርቲስቱ የተጓዘባቸው 50 ዓመታት በሀገራችን ሙዚቃ ታሪክ ውስጥ የራሱን ጉልህ ምዕራፍ የፃፈባቸው እና በዚህ ሂደትም በርካታ ውጣ ውረዶችን እንዲሁም ፈተናዎችን አልፎ ለታላቅ ስኬት የበቃባቸው አመታት ናቸው፡፡


 አሊ ቢራ ከአፈረን ቀሎ ቆይታው በኋላ ክቡር ዘበኛን ተቀላቅሎ በኦሮምኛ ሀደሬኛ ሶማሌኛ እና አማርኛ ስራዎቹን አቅርቧል፡፡ ፒያኖ ጊታር እና ኡዱ አሳምሮ የሚጫወተው አሊ ቢራ በባህር ማዶ ቋንቋዎችስዋህሊ አረቢኛ እና እንግሊዘኛም የማይረሱ ስራዎችን ተጫውቷል፡፡ አርቲስት አሊ ቢራ በእነዚህ ቋንቋዎች እስካሁን ከ260 በላይ ተወዳጅ ዘፈኖችን ሰርቷል፡፡




  አርቲሰት አሊ ቢራ ለራሱ እና ለሌሎች ድምፃውያን በርካታ ግጥም እና ዜማዎችን ደርሷል፡፡ የራሱን ለየት ያለ የአዘፋፈን ስልትም ፈጥሯል፡፡ በሀገራችን ታሪክ ታላላቅ ከሚባሉ የሙዚቃ ቡድኖች ጋርም ሰርቷል፡፡ በሀገር ውስጥ እና በውጪም በዛ ባሉ መድረኮች ላይ ተጫውቷል፡፡ በሙዚቃው ዓለም በቆየባቸው ዘመናት በሀገር ውስጥ እና በአለም አቀፍ ደረጃ የህዝብ ፍቅር እና አክብሮትን ተቀዳጅቷል፡፡ በርከት ያሉ ሽልማቶችንም አግኝቷል፡፡ ከጅማ ዩኒቨርስቲ የተሰጠው የክብር ዶክትሬትም ከእነዚህ ውስጥ አንዱ ነው፡፡

  ክቡር ዶክተር አሊ ቢራ ከሙዚቃው ጎን ለጎን “Birra Children’s Education Fund” የተባለ ምግባረ ሰናይ ድርጅት ከባለቤቱ ጋር አቋቁሞ ለህፃንት ትምህርት ድጋፍ እያደረገ ይገኛል፡፡ ድርጅቱ አሁን በድሬዳዋ አካባቢ ባሉ ት/ቤቶች ላይ እየሰራ ሲሆን በቀጣይነት በመላው የሀገሪቱ ክፍሎች የተጠናከረ ስራ ለመስራት እቅድ አለው፡፡ 


አርቲስት አሊ ቢራ እንደገለፀው ከሆነ ካሁን በኋላ እራሱን ከሙዚቃው አግልሎ በበጎ አድራጎቱ ስራ ላይ ያተኩራል፡፡ ለኦሮምኛ ሙዚቃው ንጉስ ለክቡር ዶክተር አሊ መሀመድ ቢራ እንኳን ደስ አለህ እድሜ እና ጤና ይስጥህ ፣ ያሰብከው ይሳካ ብያለሁ ……..

No comments:

Post a Comment