Monday, May 13, 2013



በአንድ ግለሰብ በተከፈተ ተኩስ 12 ሰዎች ተገደሉ


         በአንድ ግለሰብ በተከፈተ ተኩስ 12 ሰዎች ተገደሉ በባህር ዳር ከተማ ልዩ ስሙ አባይ ማዶ ወይም ቀበሌ 11 በተባለ ቦታ ትናንት ግንቦት 04/2005 ምሽት 2:45 ላይ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ባልታወቀ ምክንያት በመነሳሳት ህብረተሰቡ ሰላማዊ እንቅስቃሴውን በሚያደርግበት ወቅት በከፈተው የተኩስ እሩምታ 12 ሰዎችን ገድሏል፡፡
     ከሟቾቹ ዉስጥ ህጻናትሴቶችና አዛውንቶች  ይገኙበታል፡፡ በአደጋው የቆሰሉ ሌሎች ሁለት ግለሰቦችም ህክምና እየተደረገላቸው ነው፡፡ ድርጊቱን የፈፀመው ግለሰብ ለማምለጥ ሲሞክር በፀጥታ ሃይሎች ክትትል ሲደረስበት ራሱን ወንዝ ውስጥ መወርወሩን  የአማራ ክልል ፖሊስ አስታውቋል። ፖሊስ በጉዳዩ ላይ እያደረገ ያለውን ምርመራ እንዳጠናቀቀ ተጨማሪ መረጃ እንደሚሰጥ አስታውቋል::
    ይህ በእንዲህ  እንዳለ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤት ግድያውን አስነዋሪ የጭካኔ ተግባር ሲል አውግዞታል:: የሟቾች  የቀብር ስርዓትም በደብረ አባይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን ተፈፅሟል፡፡ በቀብር ስነ ስርዓቱ ላይ  የተገኙት የአማራ  ክልል  ርእሰ መስተዳድር  አቶ አያሌው ጎበዜም የክልሉ መንግስት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን በመግለፅ ለሟች ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተዋል ።
    
የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን  በበኩሉ በግለሰቡ ድርጊት ህይወታቸውን ባጡ ዜጎች  ህልፈተ ህይወት ምክንያት የተሰማውን ሀዘን ገልጿል ፡፡በእንዲዚህ አይነቱ  ወንጀልም በህብረተሰቡና በፖሊስ መካከል ለአመታት የቆየው መልካም ግንኙነትም አይሻክርም ብሏል በመግለጫው  ፡፡ የፖሊስነት ሙያዊ ዲስፕሊን  በጎደላቸው መሰል ፖሊሶች ይህ አይነት ክስተት ደግም እንዳይፈጠር እንደሚሰራም ያለውን ቁጥርጠኝነት አረጋግጧል ፡፡

No comments:

Post a Comment