Wednesday, July 27, 2016

ብዙዎች ቶሚ ብለው ያንቆለጳጵሱታል …. ድምፃዊ ፣ግጥም እና ዜማ ደራሲ ቶማስ አበበ፡፡

  በሙዚቃው አለም ከ3ዐ አመት በላይ አሣልፏል፡፡ በአንድ ወቅት ለአንድ ሠው ደብዳቤ ለማድረስ ሀረር ይሄዳል፡፡ በዚህ አጋጣሚ በሀረር ፖሊስ ምስራቅ ሰጎን ኦርኬስትራ ዳንስና ሙዚቃ ተፈትኖ ገና በ13 አመቱ አካባቢ የኪነ ጥበቡን አለም ተቀላቀለ፡፡ በሀረር ፖሊስ ለ3 ዓመታት ያህል ከሠራ በኋላም አዲስ አበባ ተመልሶ የቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ /የአሁኑ ብሄራዊ ትያትር/ ቤት ሰው ሊጠይቅ ይሄዳል ፡፡ እዚያም በዚሁ አጋጣሚ በትያትር ቤቱ “ዳዊት ባንድ” ውስጥ ተቀጥሮ ለትንሽ ጊዜ አገልግሏል፡፡ በዚህ ያላቆመው ይህ ሰው ፖሊስ ፣ ምድር ጦር እና ሀገር ፍቅር ኦርኬስትራዎች ውስጥም በተለያዩ ጊዜያት ገብቶ ሠርቷል፡፡ ድምፃዊ ፣ግጥም እና ዜማ ደራሲ ቶማስ አበበ፡፡

  በተፈጥሮው የዘፋኝነት ተሰጥኦ ያለው ቶማስ አበበ በልጅነቱ የጥላሁን ገሰሰ፣ በተለይም የመስፍን ሀይሌ እና ሌሎች ድምፃውያን ስራዎችን ይጫወት ነበር፡፡ ረዘም ያለውን ጊዜ በምድር ጦር ያሳለፈው ቶማስ አበበ ለራሱ ከደረሣቸው ግጥምና ዜማዎች ባሻገር ለአባይ በለጠ "ሙናዬ" እና ለታምራት ሞላ "ሙዚቃ " የተሰኙትን ድርሰቶች አዘጋጅቷል፡፡ በምድር ጦር እስከ1969ዓ.ም ድረስ በድምፃዊነት እና በግጥም እና ዜማ ደራሲነት ቆይቷል፡፡ ከዚህ በኋላ ደግሞ የኢትዮጵያ ሙዚቀኞች ማህበርን በስራ አስፈፃሚነት እና በዋና ፀሃፊነት፤ ሀገር ፍቅርን ደግሞ በህዝብ ግንኙነት ባለሙያነት አገልግሏል፡፡
 ድምፃዊ ፣ግጥምና ዜማ ደራሲ ቶማስ አበበ በደርግ ዘመነ መንግስት የሳንሱር ቀንጥጫን ቀመሷል፡፡ ቤተ መንግስት ቀርቦ ፣ ማዕከላዊን ጎብኝቶ በውህኒ ቤት ለሁለት አመት ከግማሽ በእስር ቆይቷል፡፡ እዚሁ መዲናችን አዲስ አበባ ተወልዶ ያደገው ቶማስ አበበ በግጥም እና ዜማ ደርሰቱ ፤ ራሱም ሆነ ሌሎች በተጫወቱት ስራዎቹ ማህበራዊ ሂሶችን እና ትችቶችን በመስጠት፣ ስለፍቅርም ሆነ ስለ ፖለቲካ እና ስለ ሀገር ጉዳዮች አንስቷል፡፡ እሱ ከተጫወታቸው ስራዎች መካከል “አበቦች ሲያብቡ” ፣ “የጋራ ኑሮ ነው” ፣ “ጊዜው ለጨነቀው” ፣ “ቃልሽ ይገባኛል” ፣ “መስለው እየታዪት” ፣ “ያለምንም ደም እንከኗ ይውደም” እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡

Tuesday, July 5, 2016

“የጦር ሜዳው ቀሲስ” ….. መምህር ፣ ደራሲ እና ጋዜጠኛ አበራ ለማ !!!


 አበራ ለማ  የተወለደው 1943 .. ፍቼ ሰላሌ ውስጥ ነው። እድገቱ ወሊሶንና አዲስ አበባ ያካትታል። ከኮተቤ መምህራን ማሰልጠኛ ኮሌጅም በዲፕሎማ መርሃ ግብር ከፍተኛ ውጤት በማግኘቱ “የአመቱ ታላቅ ተማሪ” የሚል ሽልማትንም አግኝቷል፡፡  በዲግሪ ፕሮግራምም ኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሑፍ ጥናት አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የማዕርግ ተመራቂ ነው። ጋዜጠኝነት ሙያ በኢትዮጵያ ሬዲዮና ፕሬስ መምሪያዎች ሠርቷል። ከጦር ግምባር ጋዜጠኝነት እስከ ኪነጥበባት ዘርፎች ሃያሲነት ዘልቋል።በጦር ሜዳ ዘገባውም “የጦር ሜዳው ቀሲስ” የሚል ቅፅል ስም ተሰጥቶት ነበር ፡፡


   እስከ 1980ዎቹ አጋማሽ ድረስ የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ዋና ጸሃፊ ሁኖ አገልግሏል። ዛሬ ኖርዌይ ነዋሪ ነው። በኖርዌይ ደራስያን ማኅበር ብቸኛውና የመጀመሪያው ጥቁርና በአፍ መፍቻ ቋንቋው የሚፅፍ አባል ደራሲ ነው። በዚህ ማኅበር ውስጥ የዓለም አቀፍ ኮሚቴው የረዥም ዘመን አባል በመሆንም ይታወቃል። ባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድህንንና (1997) ስዊድናዊ/ኤርትራ የሆነውን አስመራውን እስረኛ፣ ደራሲና ጋዜጠኛ ዳዊት ይስሐቅን (2009 ...) ሃሳብን በነጻ የመግለፅ ሽልማት እንዲሸለሙ በእጩነት አቅርቦ ማሸለሙም ይታወሳል።


ከአበራ ለማ የታተሙ ሥራዎች መካከል፡-
·         1967 ኩል ወይስ ጥላሸት እና አውጫጭኝ የግጥም መድብል፣
·         1974 ሽበት፣ የግጥም መድብል፣
·         1975 ሕይወትና ሞት፣ የአጫጭር ልብ ወለዶች መድብል፣
·         1976 ሞገደኛው ነውጤ፣ ኖቭሌት፣
·         1978 አባደፋር፣ ከሌሎች ደራስያን ጋርስብስብ፣
·         1978 ጽጌረዳ ብእር፣ ከሌሎች ገጣሚያን ጋርስብስብ፣
·         1980 የማለዳ ስንቅ፣ ያጫጭር ልቦለዶችና ግጥሞች መድብል፣
·         1980 መቆያ፣ ያጫጭር ልቦለዶችና ግጥሞች መድብል፣
·         1981 ትዝታን በጸጸት፣ ያጫጭር ልቦለዶች ትርጉም….በጋራ፣
·         1994 አውጫጭኝ፣ የግጥም መድብል፣
·       1994 ሙያዊ ሙዳዬ ቃላት፣ ኢልቦለድየቋንቋ ጉዳይ፣
·         1998 የእውቀት ማኅደር፣ ኢልቦለድጠቅላላ እውቀት፣
·         2003 E.C. ULIKE HORIZON Norsk Saksprosa samling med andre forfatterer
·         እውነትም እኛ... የግጥሞች ስብስብ ቪዲዮ በዲቪዲ፣ ታህሳስ 2003 ..
·         ጥሎ ማለፍ.....ታሪካዊ ልቦለድ፣ ጥር 2003 ..
·         ሽፈራው... ሞሪንጋ   - 2006ዓ.ም
·          “ቅንጣት - የኔዎቹ ኖቭሌቶች” - 2007ዓ.ም የሚሉት ከስራዎቹ መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ ጥቂት ድርሰቶቹም በሬዲዮ ተተርከዋል ፡፡ በተደጋጋሚ የተደመጠው እና በኢትዮጵያ ሬዲዮ በአርቲስት ፍቃዱ ተክለማሪያም አማካኝነት የተተረከው “ሞገደኛው ነውጤ” በቀዳሚነት ይቀመጣል፡፡
  

   ደራሲ ፣ ገጣሚ እና ጋዜጠኝ አበራ ለማ ከድርሰት ስራው ባሻገርም በመምህርነት ፣ በህዝብ ግንኙነት ባለሙያ እና በጋዜጠኝነት ሙያዎች በተለያዩ ተቋማት አገልግሏል፡፡ የተወሰኑ የግጥም ስራዎቹንም የተለያዩ ድምፃውያን ተጫውተውለታል፡፡ ለአብነትም ፀሀይ እንዳለ (ያሉትን ይበሉ እና ስውሩ መውደዴ) ፣ ጌታቸው ካሳ (ሀገሬን አትንኳት እና አደሴዋ) ፣ አበበች ደራራ ፣ ትዕግስት እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ አማርኛ ፣ ኦሮምኛ ፣ እንግሊዘኛ ፣ ኖሪጃን(የኖርዌ ቋንቋ) እና ፈረንሳይኛ ቋንቋዎችን ይናገራል፡፡

  ኑሮውን በኖርዌ ያደረገው አበራ ለማ ሰሞኑን ወደ ትውልድ ሀገሩ መጥቶ ስለ ስራዎቹ እና የህይወት ልምዱ ተጨዋወተን ነበር ፤ከዚህም በጥቂቱ አካፈልኳችሁ፡፡ ለጋሽ አበራ ለማ እድሜ እና ጤና ፣ በቀሪ ስራዎቹም ስኬትን ተመኘሁ፡፡ የቀረውን እናንተ ጨምሩበት …..

Saturday, April 16, 2016

“የመሰንቆው ሊቅ” ጌታመሳይ አበበ በተወለደ በ72 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ ፡፡


  የሙዚቃው ሊቅ  ጌታመሳይ አበበ በሙዚቃው ተለክፎ እጁን ለሙዚቃ የሰጠው ገና በልጅነቱ ነበር፡፡ በግል ጥረቱም ማሲንቆ የመጫወት ልምዱን አዳበረ፡፡ 1953 . ከሀገር ቤት ወዲህ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ቤት ልምምድ ሲያደርግ ከቆየ በኋላ በአንዳንድ ተፅዕኖዎች ምክንያት ትያትር ቤቱን ተሰናብቷል፡፡ 1954. (በቀድሞው የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ) በአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል የኢትዮጵያ ኦርኬስትራን ተቀላቅሎ  በድምጻዊነትና መሰንቆ ተጫዋችነት በርካታ ዘፈኖችን ተጫውቷል፡፡ የአገረሰብ የሙዚቃ ክፍል ኃላፊና አደራጅ በመሆንም አገልግለዋል።
 

   በ1960. ወደ ሀገር ፍቅር ትያትር ቤት ተዛወረ፡፡ በሀገር ፍቅር ትያትር ቤት ቆየታውም ከዘፋኝነት ባሻገር የትያትር ሙያን በመማር ከአስር በላይ በሚሆኑ ትያትሮች ከእውቅ አርቲስቶች ጋር በመሆን ተውኗል፡፡ ለአብነትም የአቤ ጉበኛየደካሞች ወጥመድ የብርሃኑ ዘሪሁንየለውጥ አርበኞችእና የጌታቸው አብዲስንት አየሁትያትሮች ከብዙ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡የመሰንቆው ሊቅጌታመሳይ አበበ 200 በላይ ዜማዎችን ተጫውቷል፡፡ በዜማ ድርሰት፣ በድምጻዊነት፣ በኃላፊነት፣ በመምህርነት እንዲሁም የባህል ቡድኖችን በመምራት በሰሜን አሜሪካ፣ በአውሮፓና በአፍሪቃ በመዟዟር የኢትዮጵያን የባሕል ጨዋታ በተለያዩ አለም አቀፍ መድረኮች እንዲንፀባረቁ እና እንዲተዋወቁ የበኩሉን ድርሻ ተወጥቷል።

   አገራዊ እሴትን፣ የአገር ፍቅርንና ጀግንነትን የሚያንጸባርቁ ሥራዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ጌታመሳይ አበበየሽምብራው ጥርጥርሆብዬ እመጣለሁየኔ አያልእናት ውብ አገሬወሸባዬዳይመኔየመኖሪያ ቤቴሰላሜ ሰላሜእና ሌሎችም አገራዊ ስሜትን ከፍ የሚያደርጉ ሥራዎቹ ተጠቃሽ ናቸው። 1996 . ባጋጠመው የጭንቅላት ዕጢ አማካኝነት ለ12 ዓመታት በህመም ላይ የቆየ ሲሆን መናገር እና መንቀሳቀስ በማይችልበት ደረጃ ይገኝ እንደነበርም ሚያዚያ 6/2008. በብሄራዊ ባህል ማዕከል ተዘክሯል፡፡ በባህል ማዕከሉ በተካሄደው የዝክር ዝግጅት ላይ በዊልቸር እገዛ ተገኝቶ የታደመው አንጋፋው ከያኒ የካባ ፣ የአገር ባህል ልብስ ፣ የዋንጫና የምስክር ወረቀት ሽልማቶችም ተበርክተውለት ነበር።


   የጠለቀ የመሰንቆ ዕውቀትና ችሎታውየመሰንቆው ሊቅየሚል መጠሪያ አጎናጽፏቸዋል። ጌታመሳይ አበበ በአሩሲ ክፍለ ሀገር ልዩ ስሙ አልባሶ በተባለ ቦታ 1935. እንደተወለደ መረጃዎች ይጠቁማሉ። አንጋፋው የጥበብ ሰው በነገው ዕለት ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ጀምሮ አድናቂዎቹ ፣ ከያኒያን እና ቤተሰቦቹ በተገኙበት በቅድስት ስላሴ ካቴድራል የቀብር ስነ ስርዓቱ ይፈፀማል፡፡ ለቤተሰቦቹ ፣ ወዳጅ ዘመዶቹ እና አድናቂዎቹ መፅናናትን እንመኛለን፡፡