Thursday, October 16, 2014

የክብር ተምሳሌቱ ……. ግመል


   የሰው ልጅ መረዳት ከቻለ በአንድም በሌላም ከእንሰሳት ጭምር ብዙ መማር ይችላል፡፡ ለአብነት ከድመት ፅዳትን፣ ከውሻ ታማኝነትን፣ ከግመል ታዛዥነትን …….. ዛሬ በአፋሮች ዘንድ የክብር ተምሳሌት ስለሆነው ግመል አንዳንድ መረጃዎችን ሳነብ ካገኘሁት ላካፍላችሁ፡፡
  

  ግመል፣ ከብት፣ ፍየል እና በግ ለአፋር ህዝብ ሀብቱ ብቻ ሳይሆኑ የህይወቱም ምሰሶ ናቸው፡፡ ከሁሉ በላይ ግን በረሃውን ለመቋቋም የተፈጠረ፣ ውሃ ጥምን ለሳምንታት የሚታገስ፣ ድርቅን ተቋቁሞ ባለቤቶቹን ክፉ ቀንን የሚያሻግር የቁርጥ ቀን እንሰሳ ነው፡፡ ግመል፡፡
 

   በአፋር በረሃ ግመልን የሚተካ የለም፡፡ ለዚህም ግመል በአፋሮች ዘንድ ከፍተኛ ክብር ይሰጠዋል፡፡ የክብር ተምሳሌትም ነው፡፡ የግመልን ያህል በብዙ ደንቦች ታጥሮ ሰውን የሚገዛ፣ ምንም የለም፡፡ ምክንያቱም ሴቶች አያልቡትም፣ በማለቢያው ሌላ አይታለብም፣ ወተቱን ማፍላት ወይም ለቅቤ መናጥ ሀራም ነው / ጥሩ አይደለም ተብሎ ይታሰባል/፡፡


   በወር አበባቸው ላሉ ሴቶች ግመልን መቅረብን እና ወተቱን መጠጣት ክልክል ነው፡፡ በአንድ ቀን ውስጥ የግመል ወተት ጠጥቶ የሌላ እንሰሳት ወተት መጠጣት ያልተገባ ነው፡፡ ቅጠላ ቅጠል ስለሚመገቡም ወተታቸው ከመድሃኒትነት ይቆጠራል፡፡


 ግመል ጥበቃ ርቀው የተሰማሩ ወጣት ወንዶች ግመል ሳይጠጣ በፊት ውሃ አይጠጡም፡፡ ሁለት ሶስት ቀን ውሃ ተገኝቶ ባይጠጣና ቢጠሙ ወተቱን አልበው ይጠጣሉ እንጂ ውሃ ከግመሉ ቀድመው አይጠጡም፡፡ ይህም በብርታት ተፈትኖ የፅናት ባህሪውን የመውረስም ምልክት ነው፡፡


  ግመል ለጭነት፣ ለወተት፣ እና ለስጋ ያገለግላል፡፡ ታዛዥነቱንም እቃ ሲጫን “ብረሂ” ሲባል በቀላሉ ከሰው ጋር ተግባብቶ የተባለውን በመፈፀም ለጭነት ይዘጋጃል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሲታረድ እንደ ሰው ድምፅ አውጥቶ ያለቅሳል፡፡ ይህም የሰውን ስሜት ይነካል፡፡በተረፈ እናንተ ጨምሩበት……..

No comments:

Post a Comment