Tuesday, September 10, 2013

ከኢትዮጵያ በማደጎ የወሰዷትን ልጅ ለሞት የዳረጉት አሜሪካውያን ቤተሰቦቿ ጥፋተኛ ተባሉ

        ኢትዮጵያዊቷን ሐና ዊሊያምስን በማደጎ ወደ አሜሪካ የወሰዳት ላሪ ዊሊያምስ በቀረበበት ሐናን የመግደል ክስ ጥፋተኛ ተባለ። በ2008 ከኢትዮጵያ በማደጎነት የተወሰደችው ሐና ከፍተኛ ቅዝቃዜ ቦታ ላይ ተቆልፎባት  የደረሰባት የጤና መታወክ ለሞት ሊዳርጋት እንደቻለ ፍርድ ቤቱ አረጋግጧል።

  ከጤና መታወክም ባለፈ ለቀናት ያለምግብ ከምድር በታች ባለ ቤት ውስጥ ተዘግቶባት  መቆየቷ ለሞቷ አንድ ምክንያት እንደሆነም ለፍርድ ቤቱ   አቃቤ ህግ ያቀረበው ማስረጃ ያመለክታል።በዚህም መነሻነት አቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ የ13 ዓመቷ ሐና ዊሊያምስን ተከሳሾቹ  አባቷ ላሪና ዊሊያምስና እናቷ ካሪ ዊሊያምስ  ከኢትዮጵያ በማደጎ በ2008 ያመጧት መሆኑን በማስረዳት ሰው በመግደል ክስ መስርቶባቸው ነበር። ሐና በ2011 ግንቦት ወር ላይ  ቤተሰቦቿ መኖሪያ ጀርባ ባለ ምድር ቤት ለቀናት ተዘግቶባት መቆየቷና የቤቱ የቅዝቃዜ ምጣኔ 4 ዲግሪ ሴልሺየስ መሆኑ ለሞት ሊዳርጋት ችሏል።

ላሪ ዊልያምስና ካሪ ዊልያምስ ከሐና ሞት ከአራት ወራት በኋላ በቁጥጥር ስር ውለው ክሳቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ሲሆን ፥ ፍርድ ቤቱም ሰው በመግደል ወንጀል ጥፋተኛ ብሏቸዋል። በተጨማሪ ተከሳሾቹ  በማደጎ የወሰዱት የ10 ዓመቱ የሐና ወንድም በተመሳሳይ የመደብደብ ፣ የርሃብና በምድር ቤት ተቆልፎበት እንደነበረም መርማሪዎች ደርሰውበታል። ለዚህም ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹን ህጻናት ላይ ጥቃት በማድረስና በአግባቡ ባለመንከባከብ ጥፋተኛ ብሏቸዋል። በቀጣዩ ወር የጥፋተኝነት ቅጣት ውሳኔ ፍርድ ቤት እንደሚያሳልፍባቸው ቀጠሮ የያዘ ሲሆን ፥ በተከሰሱበት የዋሽንግተን ግዛት ህግ መሰረት እስከ እድሜ ልክ እስራት ድረስ ሊቀጡ ይችላሉ።

                                                                                           ምንጭ: አሶሽየትድ ፕሬስ

No comments:

Post a Comment