Thursday, November 27, 2014

ለጥምቀት ጎንደር እንገናኝ …………!!!

                                          
ጥር ላይ ጎንደር ደመቅመቅ ትላለች ምክንያቱም ጥምቀት በጎንደር በልዩ ሁኔታ ይከበራልና፡፡ በርካታ የሀገር ውስጥ እና የውጪ ጎብኚዎችም ጥምቀትን በአፄ ፋሲል መዋኛ ማሳለፍን ይመርጣሉ፡፡ ለበዓሉ ወደ ጎንደር ጎራ ካሉ በበዓሉ ላይ ታድመው እግረ መንገድዎን በጎንደር ከተማም ሆነ በአቅራቢዋ የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎችን ጎብኝተው ይመለሳሉ፡፡


   የጎንደር ከተማ ዋነኛ የቱሪስት መስህብ ሀብቶች የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ነገስታት ያሰሯቸው አብያተ መንግስታት እና አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ አብያተ መንግስታቱ በከተማዋ መሀል በሚገኘው ከፍተኛ ስፍራ ላይ “የአፄ ፋሲል ግቢ” ተብሎ በሚታወቀው ሰፊ ቅጥር ውስጥ ይገኛሉ፡፡ የግቢው ስፋት 70,000 ካሬ ሜትር ይሆናል፡፡ ከ17ኛው እስከ 18ኛው ክፍለ ዘመን የነበሩ ነገስታት አብያተ መንግስታት እና ሌሎች በርካታ የህንፃ ፍርስራሾችን ይዞ ይገኛል፡፡ እነሱም፡-
1.  አፄ ፋሲል /ዓለም ሰገድ/ 1623 - 1659  የፋሲል ቤተ መንግስት/የፋሲል ግንብን/ አሰርተዋል፡፡
2.  ዮሀንስ 1ኛ /አእላፍ ሰገድ/ 1659 - 1674 ባለ ፎቅ የሆነ የቤተ መፅሀፍ አዳራሽ አሰርተዋል፡፡
3.  እያሱ 1ኛ /አድያም ሰገድ/ 1674 - 1698  የእያሱ 1ኛ ቤተ መንግስትን ››
4.  ዳዊት 3ኛ / አድባር ሰገድ/ 1708 -1713  የመዝሙር አዳራሽ ››   ››
5.  አፄ ባካፋ / መሲህ ሰገድ/  1713 - 1722  የንጉስ ባካፋ ቤተ መንግስት ››
6.  እያሱ 2ኛ / ብርሃን ሰገድ/  1722 - 1749  የእያሱ ሁለተኛ ቤተ መንግሰት ››
7.  እቴጌ ምንትዋብ / የንጉስ ባካፋ ባለቤት/ 1730 - 1755 የንግሰት ምንትዋብ ቤተ መንግሰት / ትልቅ አዳራሽ ቤት/ ያሰሩት ይጠቀሳል፡፡
   
  አብያተ መንግሰታቱ የተሰሩት ከድንጋይ፣ ከእንጨት እና ከኖራ ሲሆን ድንጋዩም ቀላ ያለና ልስላሴ ያለው የተጠበሰ ሸክላ የመሰለ ነው፡፡ ይገኝ የነበረውም ቁስቋም እና ጅብ ዋሻ ከሚባሉ ስፍራዎች እንደነበር ይነገራል፡፡ 
  በአፄ ፋሲል ግቢ ከሚገኙ ህንፃዎች ትልቁ እና ከሞላ ጎደል በደህና ሁኔታ ላይ የሚገኘው የአፄ ፋሲል ቤተ መንግስት ነው፡፡ 32 ሜትር ርዝመት እና 3 ፎቆች እንዲሁም በርካታ የምድር ውስጥ ክፍሎች አሉት ፡፡ ከመጨረሻ ፎቅ በስተ ደቡብ ምዕራብ ላይ በከበሮ ቅርፅ የተሰራ ክፍልም አለ፡፡የህንፃው አራት መአዘን አናቶች የግማሽ እንቁላል ቅርፅ አላቸው፡፡ በተለምዶ የእንቁላል ግንብ ተብለው ይጠራሉ፡፡ እነዚህ የአፄ ፋሲል ቤተ መንግሰት ግብረ ህንፃዎች ጥቅምት 26, 1979 እ.ኤ.አ የተባበሩት መንግስታት የትምህርት ፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት/ ዩኔስኮ/ በአለም ቅርስነት መዝግቧቸዋል፡፡


   ከአፄ ፋሲል ግቢ ውጪ በተመሳሳይ ዘመን የኪነ ህንፃ ጥበብ የተሰሩ በርካታ ህንፃዎችም  ይገኛሉ፡፡ የአፄ ፋሲል መዋኛ፣ በቁስቋም የሚገኘው የእቴጌ ምንትዋብ ግቢ፣ የራስ ሚካኤል ስሁል ግቢ እና የደብረ ብርሃን ስላሴ ዋነኞቹ ናቸው፡፡

No comments:

Post a Comment