Saturday, May 23, 2015

የአበጋር የግጭት አፈታት ስነ ስርዓት...


  አበጋር ማለት ባህላዊ የግጭት መፍቻ ስርአቱ ተቋም መጠሪያ ስያሜ እና የዳኛነት ስርአቱን የሚከውኑ ግለሰቦች የማዕረግ ስም ነው፡፡ አበጋር በሚኖሩበት አካባቢ ማህበረሰብ ውስጥ የሚከሰቱ የተለያዩ ግጭቶችን የመፍታትና የማስታረቅ ስልጣንና ይሁንታ ያገኙ ሰዎችን የያዘ ተቋም ነው፡፡ ተቋሙ ከአነስተኛ ግጭት እስከ ከፍተኛው የግድያ ወንጀል ድረስ ያሉ ግጭቶችን በየደረጃው የመፍታት ስልጣን አለው፡፡ ይህ ተቋም ወንዶች ብቻ የሚሳተፉበት ነው፡፡
  
  አበጋርነት ማዕረግ በሁለት መንገድ ይገኛል፡፡ የመጀመሪያው ከዘር የሚወረስ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በመመረጥ ይገኛል፡፡ በዘር የሚገኘው አበጋርነት ከጥንት ጀምሮ ከአባት ወደ ወንድ ልጅ በቅብብሎሽ የሚወረስ ነው፡፡ ወንድ ልጅ የሌለው አበጋር ለሴት ልጁ ማውረስ አይችልም፡፡ ነገር ግን አበጋሩ ለመረጠው የወንድሙ ወይም ለእህቱ ወንድ ልጅ ማውረስ ይችላል፡፡  አበጋሩ የሚተካውን አካል የመምረጥ እና የማብቃት እንዲሁም እድሜው መድረሱን ያረጋግጣል፤ ተተኪው አበጋር የማመዛዘን ብስለቱ እንዲያድግ እና ትክክለኛ ፍርድ እንዲሰጥ እድሜው 30 እና ከዚያ በላይ መሆን ይኖርበታል፡፡

  ሁለተኛው የአበጋርነት ማዕረግ ደግሞ በመመረጥ የሚገኝ ነው፡፡ ከአካባቢው ማህበረሰብ መካከል ተደማጭነት ፣ ተቀባይነት ፣ የሚከበር እና ተግባቢነት ያለውን ግለሰብ ማህበረሰቡ በመምረጥ እና በመሰየም የሚሰጠው ማዕረግ ነው፡፡ የተመረጠው አበጋር በተለያዩ ሁኔታዎች የተሰጠውን ኃላፊነት በአግባቡ መወጣት ካልቻለ ሌላ የመምረጥመ ሆነ የመተካት ስልጣን ያለው የአካባቢው ማህበረሰብ ነው፡፡ በዘር እንደሚገኘው የአበጋርነት ማዕረግ ለወንድ ልጁ ወይም ለሌላ አካል ስልጣኑን ማውረስ ወይም ማስተላለፍ አይችልም፡፡

  አበጋር የሰላም አባቶች ናቸው፡፡ ደም የተቃባን ያስታርቃሉ ፣ ደም ያደርቃሉ፡፡ አብዛኛው የወሎ ህዝብም የሀይማኖት ልዩነት ሳይገድበው በአበጋር ይዳኛል፡፡ አበጋሮች /ሽማግሌዎች/ የሟች እና የገዳይን ቤተሰብ ያቀራርባሉ፡፡ የአበጋርን የሰላም ፣ የእርቅ ጥሪ አልቀበልም የሚል አይኖርም ፤ ቢኖርም ከህብረተሰቡ ይገለላል፡፡ የአበጋር የእርቅ ስነ ስርዓት በሁሉም ህብረተሰብ ይከበራል፡፡ በአጠቃላይ አበጋር የዘመመ ጎጆን ፣ የፈረሰ ትዳርን ያቃናል፡፡


  አበጋርም ሆነ ሌሎች  ባህላዊ ዳኝነቶች እና የእርቅ ስነ ስርዓቶች ሊጎለብቱ እና ሊያድጉ ይገባል፤ ምክንያቱም ዘመናዊውን የፍትህ ስርዓት ያግዛሉና፡፡

   ምንጭ ፡-  በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቋንቋና የባህል እሴቶች ልማት ዳይሬክቶሬት

No comments:

Post a Comment